አይሮፕላን ጣቢያዎችና የሃገሪቱ የአየር ክልል የበረራ ደኅንነት የተጠበቀ መሆኑን ሲቪል አቪየሽን አስታወቀ

.

የኢትዮጵያ ሲቪል አቪየሽን ባለሥልጣን ዛሬ ባወጣው መግለጫው “በመገናኛ ብዙኃን እየተዘገበና እየወጣ ያለው ማስጠንቀቂያ መሠረተ ቢስና በእውኑ ካለው እውነታ ጋር ፍፁም ተፃራሪ ነው” ብሏል።

የዩናይትድ ስቴትስን ፌደራል አቪየሽን አስተዳደር ከትናንት በስተያ ለአብራሪዎች አወጣ ያለውን ማሳሰቢያ ጠቅሶ አሶሽየትድ ፕሬስ ትናንት ባወጣው ዘገባ “በአፍሪካ እጅግ የበዛ ትራፊክ ካላቸው አይሮፕላን ጣቢያዎች አንዱ የሆነው አይሮፕላን ጣቢያ በቀጥታም ይሁን ቀጥተኛ ባልሆነ ሁኔታ ለምድር ላይ ተኩስ ወይም ከምድር ወደ አየር ለሚተኮሱ መሳሪያዎች ሊጋለጥ እንደሚችል” ተናግሮ ነበር።

ይሁን እንጂ “የአዲስ አበባ ዓለምአቀፍ አይሮፕላን ጣቢያን ጨምሮ የኢትዮጵያ የአየር ክልል ለበረራ ደኅንነቱ የተጠበቀ ነው” ያለው የኢትዮጵያ ሲቪል አቪየሽን ባለሥልጣን “የአየር ክልላችንንም ሆነ አይሮፕላን ጣቢያዎቻችንን ደኅንነትና ፀጥታ ለአደጋ እንደማናጋልጥ ለተገልጋዮች ሁሉ አጥብቀን እናረጋግጣለን” ብሏል።

ባለሥልጣኑ በዚሁ መግለጫው አክሎም የበረራ እንቅስቃሴዎች ደኅንነት የተጠበቀ መሆኑን ለማረጋገጥ እንደበፊቱ ሁሉ ማንኛውንም እርምጃዎች እንወስዳለን” ብሏል።

የደኅንነትና ፀጥታ ጥበቃ ዓለምአቀፍ ደረጃዎችን እንደሚያከተልም ባለሥልጣኑ በዚሁ አጭር መግለጫው አስታውቋል።

Your browser doesn’t support HTML5

አይሮፕላን ጣቢያዎችና የሃገሪቱ የአየር ክልል የበረራ ደኅንነት የተጠበቀ መሆኑን ሲቪል አቪየሽን አስታወቀ