አብዛኛውን ጽንስ የማቋረጥ አገልግሎት የሚከለክለው የቴክሳስ ሕግ እንዲታገድ የቀረበው አቤቱታ በዩናይትድ ስቴትስ ጠቅላይ ፍርድቤት ውድቅ ተደረገ፡፡ ሕጉ በዩናይትድ ስቴትስ ሁለተኛ ግዙፍ ግዛት እንደሆነች በሚነገረው በቴክሳስ ጽንስን በማቋረጥ ጉዳይ ላይ የሴቶችን የመወሰን መብት በብዙ የሚቀንስ እንደሆነ ተነግሯል፡፡
ከረቡዕ እለት ጀምሮ ተግባራዊ መደረግ የጀመረውን ጽንስን ማቋረጥን የሚከለክለውን የቴክሳስ ሕግ ለማስቆም ከአገልግሎት ሰጪዎችና ከሌሎች የቀረቡለትን የይግባኝ አቤቱታ ጠቅላይ ፍ/ቤቱ 4 ለ 5 በሆነ ድምጽ ውድቅ አድርጎታል፡፡ ሪፐብሊካኑ ሃገረ ገዥ ግሬግ አቦት ባለፈው ግንቦት የፈረሙበትና ያጸደቁት ይህ ሕግ ጽንስ የልብ ትርታ እንዳለው ሃኪሞች ካረጋገጡበት ጊዜ ጀምሮ ማቋረጥ እንደማይቻል የሚደነግግ ነው፡፡
ያ ጊዜ ደግሞ ብዙ ሴቶች መጸነሳቸውን እንኳን ላያውቁ የሚችሉበት ወደ ስድስት ሳምንታት የሚሆን ጊዜ በመሆኑ ብዙዎችን ሲያነጋግርና ሲያነታርክ ቆይቷል፡፡
አዲሱ የቴክሳስ ሕግ 'የ ሮቪ ዌድ' ተብሎ የሚታወቀውን የዛሬ 48 ዓመት በአውሮፓዊያን ዘመን አቆጣጠር በ1973 ዓ.ም በጠቅላይ ፍ/ቤቱ የተላለፈውን ጽንስን የማቋረጥ መበት ውሳኔ ለመገዳደር ከወጡ ሕግጋት እጅግ የጠበቀው እንደሆነ የሚነገር ሲሆን ሪፐብሊካኑ የያዙት በመላ ሃገሪቱ ጽንስ እንዲቋረጥ የሚያደርግ ጥረት አካል መሆኑ ይታወቃል፡፡
ይሁን እንጂ ከሕጉ ጋር የተያያዙ ሌሎችም ክሶችና አቤቱታዎች ገና ውሳኔ ያልተሰጣቸው በመሆኑ ይህ የፍርድ ቤቱ ውሳኔ የግዛቲቱ ሕግ ጸንቶ ስለመቆሙ ማረጋገጫ እንደማይሰጥ ዳኞቹ ተናግረዋል፡
ቢያንስ 12 የሚሆኑ ግዛቶች በጽንስ መጀመሪያ አካባቢ ማቋረጥን የሚከለከሉ ሕግጋትን ቢያወጡም ሁሉም በጠቅላይ ፍ/ቤቱ እየታገዱ ተግባራዊ ሳይደረጉ ቀርተዋል፡፡ ምንም እንኳን የይታገድልን አቤቱታው በአብላጫው ዳኞች ውድቅ ቢደረግም ዋናው ዳኛ እንዳሉት ውሳኔው በጉዳዩ የቴክሳሱን ሕግ ሕገመንግስታዊነት የሚያረጋግጥ ተደርጎ ሊወሰድ እንደማይችል አስታውቋል፡፡
ዝርዝሩን ከተያያዘው የድምጽ ፋይል ያድምጡ፡፡